Friday, May 22, 2015

እነሆ የኛ ሙከራ ምርጫ የመጨረሻው ውጤት! – አቤ ቶኮቻው

10985348_942394589138617_4438841114629368036_nድንጋይ ነክሼ እምላለሁ ምንም አላጭበረበርኩም፤ በአጠቃላይ ከአንድ ሺህ አንድ መቶ በላይ ሰዎች ምርጫ አድርጉ ብዬ በለጠፍኩት ላይ አሰተያየት ሰጥተዋል። በዚህ ፌስ ቡክ አካውንት 567 አካባቢ እና በፌስ ቡክ ገጻችን 537 አካባቢ። ከነዚህ ውስጥ ግን ይሄ የእከሌ ድምጽ ነው ተብለው ለመቆጠር የቻሉት ሰባት መቶ አርባ አንዱ ናቸው። በተቻለኝ አቅም ድግግሞሽ እንዳይኖር ሙከራ አድርጌያለሁ…
በነገራችን ላይ በርካታ የምርጫ አፕልኬሽኖች ቢኖሩም እነርሱን ያለመረጥኩበት ምክንያት እግረ መንገዳችንን አስተያየቶችን እንስማ ማን ሰለማን ምን አስተያየት አለው፣ እንዴትስ ይገለጸዋል የሚለውን ለማየት ነው… ሪሰርቸሮች ”Qualitative” ወደሚሉት የሚጠጋ መረጃ አሰባሰብ በሉት! በአፕሊኬሽኑ ምርጫ ብናደርግ ግን ‘‘Quantitative” ወይም ቁጥር ብቻ ነበር የሚሆንብን! ስለተሰጡን አስተያየቶች ሌላ ቀን ብንለውም ለአሁን ግን በተለይ ትላንት ናሙና ውጤት ካወጣን በኋላ በርካታ የመድረክ ደጋፊዎች ድምጻቸውን ሰጥተው ከሰማያዊ ቀጥለው ሁለተኛ ሆነዋል።
ሰማያዊ ፓርቲ ከትላንቱ ናሙና ውጤት ጭማሪ አሳይቶ ሰባ አንድ በመቶ ተመርጧል። መድረክ አስራ ሁለት በመቶ ሲመረጥ፤ ኢህአዴግ አስራ አንድ በመቶ ድምጽ አግኝቷል። (ወይ ይቺ አስራ አንድ በመቶ… በውነት መድረክ ስለበለጠው ግን ደስ ብሎናል…. ነውር አይደለም እንዴ በሜዳቹ (በኢቲቪ አሸንፈናቹ በሜዳችን ፌስ ቡክ ስንበለጥ) ኤዴፓ አሁንም ከአንድ በመቶ ማለፍ አልቻለም። መልሱ የለም የሚለውን የመረጡ ሰዎች አምስት ፐርሰንት ሆነዋል።
በነገራችን ላይ ትግስት እና ጊዜ ያለው ሰው በፌስ ቡካችን ሁለት ፖስቶች እና በፌስ ቡክ ገጻችን ሁለት ፖስቶች የተሰጡ አስተያየቶችን ለቅሞ በመቁጠር ማረጋገጥ ወይም …እኔስ ታዘብኩሽ ብሎ መታዘብ ይችላል። በበኩሌ ግን ድንጋይ ነክሼ እምላለሁ በሀቀኝነት በታማኝነት እና በታታሪነት ነው ቆጠራ ያደረኩት!
ይሄ ምን ያሳየናል… ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው።
ይሄ የሚያሳየን በርግጥም የኔን ፖስት የሚያዩት አብዛኛዎቹ ወዳጆች የሰማያዊ ፓርቲ ደጋፊዎች መሆናቸውን ሊሆን ይችላል፣ ነገር ግን ከቁጥራቸው መብዛት አንጻር ሲታይ በተወሰነ መልኩ የመሬቱ ነጸብራቅም የመሆን እድሉ ሰፊ ነው።
ተሳትፎ ያደረጋችሁ ወዳጆች በሙሉ ምስጋናዬ ከፍ ያለ ነው… ሌሎቹን ጉዳዮች ቅዳሜ በምንቀርጻት ዋዛ እና ቁምነገር ላይ እናነሳሳቸዋለን!

No comments:

Post a Comment