Sunday, May 31, 2015

ከገዢዎቻችን ለምን አንማርም ? – ግርማ ካሳ

ethiopian-election-2015“ኢህአዴግ የግንቦት15ቱን ምርጫ መቶ በመቶ ማሸነፉ ከተገለጸ በሁዋላ የኢህአዴግ ደጋፊዎች ከሁለት ተከፍለዋል። ምንጮች እንደገለጹት በርካታ ፊደል ቀመስ አባሎቹ ኢህአዴግ አሸነፍኩ ያለበትን የድምጽ ልዩነት አልተቀበሉትም። ውጤቱን የሚቃወሙ የግንባሩ አባላት ” ህዝቡ ከእንግዲህ በሰላም መንግስት እቀይራለሁ የሚለው እምነቱ ተሟጦ የሃይል አማራጭን ብቻ እንዲመለከት ከማድረጉም በላይ፣ የሃይል አማራጭን የሚከተሉ ሃይሎች በህዝቡም ሆነ በአለማቀፉ ማህበረሰብም የተሻለ ተቀባይነት እንዲያገኙ ያደርጋቸዋል” በማለት ለድርጅቱ አስተያየታቸውን እየሰጡ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ተገኘ የተባለውን ውጤት ከመደገፍ አልፈው፣ ህዝቡ እንዴት ለተቃዋሚዎች ይህን ያክል ድምጽ ሊሰጥ ቻለ በማለት በቁጭት አስተያየት የሚሰጡ ደጋፊዎች መኖራቸውንም ምንጮች ገልጸዋል።”
የሚከተለው ኢሳት ከዘገበው የተወስደ ነው። ዜናውን ለመቀበል አላዳገተኝም። “የሰላም በር ሲዘጋ የአመጽ በር ይከፋታል” እንዳለው አብርሃ ደስታ፣ ፍጹም አሳፋሪ የሆነው የምርጫው ሂደትና የምርጫው ዉጤት፣ ብዙ ዜጎች ሰላማዊዉን እና ሕጋዊዉን መንገድ ትተው ሌላ የትግል አማራጭ እንዲከትሉ ነው የገፋፋቸውና የሚገፋፋቸው።
ሆኖም አንድ ነገር ጠንቅቀን ማወቅ አለብን። መለስ ዜናዊ የሞተ ጊዜ ተከፋፈሉ ወዘተረፈ እያልን ስናወራ ነበር። ግምገማ ተደራረጉ ብለንም ስለነርሱ ስንተነትን ጊዜ አጠፋን። ምናልባት እነርሱ እርስ በርስ ከተከፋፈሉ በግርግር ለዉጥ ይመጣል ከሚል ተስፋ።
ሰዎቹ እርስ በርስ ይጠማመዱ ይሆናል። ነገር ግን መቼም አይለያዩም። ያውቃሉ፣ አንዱ ከወደቀ ሌላዉም እንደሚውድቅ። እነ አባዱላ ፣ እነ አዲሱ ለገሰ፣ እነ ሬድዋን ሁሴን ፣ ሕወሃት ከሌለ የነርሱ እጣ ምን ሊሆን እንደሚችል ይዉቃሉ። ስለዚህ አንዱ በአንዱ ላይ እንደ መዥገር ተጣብቆ ነው የሚጓዙት። ሥር የሰደደም ልዩነት ቢኖራቸውም፣ ተያይዘው ፣ ጀርባ ለጀርባ እየተታከኩ የግፍ አገዛዙን ይቀጥላሉ።
በነርሱ መካከል እርስ በርስ ልዩነቶች ተፈጥረው፣ ሞደሬት የሆኑት አይለው ቢወጡና አገር መረጋጋት ብትችል ደስ ነው የሚለኝ። ግን የሚሆን ነገር አይደለም። እነርሱ አይለያዩም። አንድ ናቸው።
በተቃራኒው እኛ ግን ትናንሽ ልዩነቶች እያለያዩን በጋራ መንቀሳቀስ አልቻልንም። በአገር ቤት ሰማያዊ፣ አንድነት፣ መኢአድ ፣ ትብብር …እንዲሁም ሌሎች ለምን በአንድ ላይ መስራት አልቻሉም ? መድረኮች ከነሰማያዊ ጋር ለምን መስራት አልቻሉም ? ወደ ዉጭ አገር ስንመጣ ደግሞ ሸንጎ፣ የሽግግር ምክር ቤቱ፣ ግንቦት ሰባት፣ ሶሊዳሪቲ ….ለምን አብረው ፣ አንድ አማራጭ ኃይል አቋቁመው መስራት አልቻሉም? ሁሉም ነጻነት ፈላጊ አይደሉም እንዴ ? ሁሉም ፍትህና ዴሞክራሲን ናፋቂ አይደሉም እንዴ ? ሁሉም ለአንዲት ኢትዮጵያ የቆሙ አይደሉም እንዴ ? ታዲያ ለምን መተባብር ቸገራቸው ?
ወገኖቼ, ደግሜ እላለሁ ገዢዎቻችን አይለያዩም። እነርሱ አንድ ሆነው፣ እኛ ደግሞ ተለያይተን እስከቀጠልን ድረስ ረግጠው፣ አዋርደው ይገዙናል። አራት ነጥብ። በተናጥል በባዶ፣ እንጮሃለን፣ እንኮንናችቸዋለን፣ ዘራፍ እንላለን ፣ የመግለጫ ዉርዥብኝ እናወርዳለን ። ግን የምናመጣው ነገር አይኖርም።
ስለዚህ ለዉጥ ክአገዛዙ ከራሱ ቢመጣ እስየው። ስንማጸንና ስንጎተጎት የነበረ ስለሆነ። ሆኖም ከአሁን በላይ ተስፋን እነርሱ ላይ ሳይሆን፣ አምላካችን እና አምላክ በሰጠን የተባበረው ክንዳችን ላይ መሆን ነው ያለበት። እመኑኝ ስርዓትቱ የበሰበሰ ስርዓት ነው። ገና ድሮ መወገድ የሚችል ስርዓት ነበረ። እስከ አሁን የቆየው እኛ ስለፈቀድንለት ብቻ ነው። አሁንም በአንድነት መንቀሳቀስ ካልቻልን፣ በአፋችን ብንናገረዉም ስርዓቱ እንዲቀጥል እየፈቀድንለት ነው።
ገዢዎቻችን ለክፋት አንድ ከሆኑ፣ እኛ ለመልካም ነገር እንድ መሆን እንዴት ያቅተናል ?

No comments:

Post a Comment