(ዘ-ሐበሻ) በጎጃም ፍኖተ ሰላም ከተማ የተጀመረው ሕዝባዊ ተቃውሞ ዛሬም በመቀጠል ከተማዋ በተኩስ እሩምታ ስትታመስ መዋሏን ምንጮች ዘገቡ:: እንደምንጮች ዘገባ ዛሬ አንድ የትግራይ ነጻ አውጪ ሰራዊት ተላላኪ ታጣቂ በቀበሌ 03 አንድን ሰላማዊ ወጣት ገድሎ ሌሎችን ሲያቆስል በአጸፋው ሕዝብ የዚህን ታጣቂ መኖሪያ ቤት እንዳነደደው ተዘግቧል::

ለፍኖተ ሰላም ከተማ ቅርብ በሆነችው ጅጋ ከተማም በተደረገ ተቃውሞ አንድ ወጣት በትግራይ ነጻ አውጪ ሰራዊት መገደሉ ሲሰማ ከተማው በተቃውሞ ሲናጥ ውሏል:: ፍኖተሰላምን ተሻግሮ በቡሬ ከተማ እና በግንደወይን የአማራው ተቃውሞ አይሎ ሲውል አካባቢውን የትግራይ ነጻ አውጪ መንግስት ወታደሮች ከበውታል:: ሆኖም ግን ሕዝቡ ምንም ሳይፈራ ተቃውሞውን በማሰማት ላይ ነው:: እንደምንጮች ገለጻ ሠራዊቱ ወደ ሕዝቡ የተኮሰ ሲሆን ምን ያህል ሰው እንደተጎዳ ለማወቅ አልተቻለም::
ይህ በጎጃም የተነሳው ተቃውሞ በማንኩሳ ከተማም እየደረገ ሲሆን የትግራይ ነጻ አውጪ ሰራዊት አንድ ሰላማዊ ሰው መግደሉና በርካቶችን ማቁሰሉን የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ:: ይህ የአማራው ተቃውሞ በሞጣና ቢቸና ከተምችም ይዛመታል በሚል ከተሞቹ በከፍተኛ ጥበቃ ስር ሲሆኑ አካባቢው ውጥረት መንገሱም ታውቋል::
በሌላ በኩል ኮለኔል ደመቀ ዘውዱን ከጎንደር ማረሚያ ቤት ለመውሰድ የመጣው የትግራይ ነጻ አውጪ ሰራዊት በማረሚያ ቤት ፖሊሶች አንሰጣችሁም በመባላቸው ወደ መጡበት እየተመለሱ መሆኑ ተሰምቷል:: እንደ መረጃው ከሆነ ትናንት ኮለኔል ደመቀ ዘውዱ አንሰጥም በሚል በተነሳ ግጭት ከተማዋ ለሊቱን ሙሉ በተኩስ ስትናጥ አድራለች:: በመላው ጎንደር አሁንም ውጥረቱ እንዳለ ሲሆን ሕዝብ አንገዛም ባይነቱን እንደቀጠለ ነው::
No comments:
Post a Comment